አርእስተ ዜና
Fri. May 3rd, 2024

የፍጥነት መንገድ ሃብትና ንብረት የዘረፉ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ

Sep25,2022
የፍጥነት መንገድ ሃብትና ንብረት የዘረፉ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉየፍጥነት መንገድ ሃብትና ንብረት የዘረፉ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ

ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር የአዲስ-አዳማ የፍጥነት መንገድ ሃብትና ንብረት የዘረፉ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉ ተገለፀ፡፡

የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ከሚያስተዳድራቸው የፍጥነት መንገዶች አንዱ የሆነው እና አገልግሎት መስጠት ከጀመረ ከሰባት ዓመት በላይ የሆነው የአዲስ-አዳማ የፍጥነት መንገድ ያልተቋረጠ የ24/7 የክፍያ መንገድ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡

ደህንነቱ የተጠበቀ፤ ምቾቱ የተረጋገጠ እንዲሁም ዘመናዊ እና አስተማማኝ አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘው የአዲስ-አዳማ የፍጥነት መንገድ በተለያዩ ጊዜ የሚገጥሙትን ተግዳሮቶች በማለፍ ስኬታማ ጉዞ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

ይሁን እንጂ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በመንገዱ ላይ በተለያየ ጊዜ የፀጥታ ስጋቶች እና የስርቆት ወንጀሎች እየተፈፀሙ ክትትል ሲደረግባቸው የቆዩ ሲሆን ወንጀለኞችን ተከታትሎ ለሕግ በማቅረብ ረገድ ፖሊስ ሰፊ ስራ ሲሰራ ቆይቷል፡፡

ለኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አባላት ነሐሴ 22 ቀን 2014 ዓ.ም ከሌሊቱ 5፡30 በደረሳቸው መረጃ መሠረት በፍጥነት መንገዱ ላይ የብረት አጥር እና የሴፍቲ መልዕክት ማስተለለፊያ ቦርዶች ላይ ስርቆት ሲፈፀሙ እጅ ከፍንጅ ተይዘው ነሐሴ 22 ቀን 2014 ዓ.ም ከቀኑ 9፡00 ገደማ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ በተጠርጣሪዎች ላይ በተደረገው ብርበራ በአዳማ ከተማ፣ ሉጎ ክፍለ ከተማ ቀጠና ሦስት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ከክፍለ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት ጋር በመቀናጀት ግምታቸው ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን የመንገድ ሃብትና ንብረቶች በቁጥጥር ስር ማዋል ተችሏል፡፡

ተጠርጣሪዎቹን ተከታትሎ ለመያዝ ከማህበረሰቡ ጋር የተደረጉ ውይይቶች በመንገዱ ዙሪያ ካሉ የከተማ አስተዳር የፀጥታ ዘርፎች ጋር የተሰሩ ስራዎች ያደረጉት አስተዋፅኦ እንዳለ ሆኖ በተለይ ንብረቶቹን ተከታትለው በቁጥጥር ስር ያዋሉት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አባላት፣ የአዳማ ከተማ፣ ሉጎ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት፣ ከኢንተርፕራይዙ ጋር የሚሰሩ የኦሮሚያ ፖሊስ አባላት እንዲሁም የኢንተርፕራይዙ ፀጥታ ዘርፍ ጋር በመቀናጀት እንደሆነ ተገልጿል፡፡

በቀጣይም ኢንተርፕራይዙ ከፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት የወንጀሉ ፈጻሚዎችን ለሕግ አስኪቀርቡ ድረስ ክትትሉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል እያሳወቀ አሁን ለተገኘው ውጤት ሕብረተሰቡ፣ የፀጥታ አካላትና የከተማ አስተዳደሮች ላደረጉት ርብርብ ምስጋናውን አቅርቧል ፡፡
የመረጃ ምንጭ – ETRE

Related Post