አርእስተ ዜና
Fri. Apr 26th, 2024

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ተጨማሪ 15 ሕይወት ጠፋ

Sep25,2020
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ተጨማሪ 15 ሕይወት ጠፋ

“የዜጎችን ደሕንነት ማረጋገጥ እና ወንጀለኞችን ለፍርድ ማቅረብ ያስፈልጋል! – በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በድጋሚ በተፈፀመ ጥቃት ቢያንስ የ15 ሰዎች ሕይወት ማለፉ በእጅጉ አሳሳቢነቱን እንደጨመረ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ገለጸ፡፡

ዛሬ መስከረም 15 ቀን 2013 ዓ.ም ከንጋቱ 11 ሰዓት ገደማ በመተከል ዞን፣ ዳንጉር ወረዳ፣ ማንቡክ ከተማ በንገዝ ወንዝ አካባቢ በሚገኝ መንደር በታጠቁ ሰዎች በተከፈተ ተኩስ የ15 ሰዎች ሕይወት ማለፉን ኮሚሽኑ አረጋግጧል፡፡

እስከ ዛሬ ቀኑ 8 ሰዓት ድረስ በተሰበሰበ መረጃ፤ 15 ያልታጠቁ ሲቪል ሰዎች ህይወት ማለፉን እና ከሟቾች መካከልም 11 ወንዶች እና 4 ሴቶች መሆናቸውን ከአካባቢው ካሉ የመንግስት ምንጮች ኮሚሽኑ አረጋግጧል፡፡ የሟቾች እድሜ እስካሁን ያልተለየ ሲሆን በተጨማሪም አንድ ሰው ለሕይወት የማያሰጋ መቁሰል እንደደረሰበት ተመሳሳይ ምንጮች ለኮሚሽኑ አስረድተዋል፡፡ የአገር መከላከያ ሰራዊት አሁንም የተጎዱ ሰዎችን ለማፈላለግ አሰሳ እያካሄደ ሲሆን ምናልባት የተጎዱ ሰዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ስጋት መኖሩን ለማወቅ ተችሏል፡፡

እስካሁን ያሉ መረጃዎች ጥቃቱ የተፈጸመው በሕገ ወጥ ታጣቂዎች እንደሆነ የሚያመለክቱ ሲሆን ኮሚሽኑ በደረሰው መረጃ መሰረት ታጣቂዎቹ ከመከላከያ ሰራዊት ጋር የተኩስ ልውውጥ ካካሄዱ በኋላ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ የመከላከያ ሰራዊት አካባቢውን እንደተቆጣጠረ ለማረጋገጥ ችሏል፡፡

የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) ‹‹ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጸጥታን ማስፈን፣ የሕግ በላይነትን ማረጋገጥና በሲቪል ሕዝብ ላይ አሰቃቂ ጥቃት እያደረሱ ያሉትን አጥፊዎች አድኖ ለፍትሕ ማቅረብ እጅግ አፋጣኝ ትኩረት ይሻል›› ብለዋል፡፡

ከትላንት መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ የመተከል ዞን አራት ወረዳዎች የፀጥታ ኃላፊነት እስከ ህዳር 2013 ድረስ በኮማንድ ፖስት ስር እንዲሆን በተሰጠ ውሳኔ መሰረት የጸጥታ ማስከበሩን ስራ የፌደራል መንግስት ተረክቧል፡፡ በኮማንድ ፖስቱ ስር የሚቆዩት ትናንት ንጋቱ ላይ ጥቃት ያጋጠመው የዳንጉር ወረዳን ጨምሮ የወምበራ፣ ቡለን እና ጉባ ወረዳዎች ናቸው ፡፡
(ምንጭ – የኢሰመኮ ጋዜጣዊ መግለጫ)

Related Post