አርእስተ ዜና
Sat. May 4th, 2024

የኢዲስ አበባ ባዶ ቦታዎች በዚህ ዓመት ይታረሳሉ

May15,2020
የኢዲስ አበባ ባዶ ቦታዎች በዚህ ዓመት ይታረሳሉየኢዲስ አበባ ባዶ ቦታዎች በዚህ ዓመት ይታረሳሉ

በኢዲስ አበባ ከተማ በመንግስትም ሆነ በግለሰብ ታጥረው የተቀመጡ ባዶ ቦታዎች ታርሰው ለግብርና ልማት እንደሚውሉ የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ ተናገሩ።

ከተማ አስተዳደሩ የከተማ ግብርናን ለማገዝ የሚያስችሉ 200 የውሃ ፓምፖች እና 5 ትራክተሮችን በአምስት ክፍለ ከተማዎች ለሚገኙ አርሶ አደሮች አበርክቷል። በዚሁ ወቅት ምክትል ከንቲባው ኢንጂነር ታከለ እንደገለጹት፤ በኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ የተነሳ በዚህ ዓመት ሊያጋጥም የሚችለውን የምርት ክፍተት ለማሟላት የተለያዩ ተግባራት ይከናወናሉ። ”በዚህ መሰረት ታጥረው የሚገኙ ባዶ ቦታዎች ለከተማ ግብርና ልማት እንዲውሉ ይደረጋል” ብለዋል።

በከተማዋ በኑሮ ውድነትን የሚደርሰውን ጉዳት ለመቆጣጠርና በተመጣጣኝ ዋጋ ምርት ለማቅረብ በአስምት አካባቢዎች ላይ የገበያ ማዕከላት እየተገነቡ እንደሆነም ጠቁመዋል። ”አርሶ አደሮች በተሻለ ዋጋ ምርቶቻቸውን እንዲሸጡ፤ ነዋሪዎችም በተመጣጠኝ ዋጋ እንዲሸምቱ ያስችላል” ብለዋል። የውሃ ፓምፕ የተበረከተላቸው የከተማዋ አርሶ አደሮች የማምረቻ መሳሪያዎቻቸውን በመዋዋስ የተሻለ ምርት ለማምረት እንዲሰሩም መልዕክት አስተላልፈዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ኮሚሽን ኮሚሽነር ወይዘሮ ፈቲያ መሐመድ በበኩላቸው ”የከተማ ግብርናን በማዘመን የከተማዋን 25 በመቶ ህዝብ የምግብ ፍላጎት ለማሟላት እየተሰራ ይገኛል” ብለዋል።

”ከዚህ በፊት የከተማ ልማት ሲካሄድ አርሶ አደሩን የሚያቅፍ ያልነበረ ነው” ያሉት ወይዘሮ ፈቲያ፤ የልማት ስራዎች አርሶ አደሩን ታሳቢ አድርገው እንደሚካሄዱ ገልጸዋል። ከ5 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ብድር እንደተመቻቸላቸውና 1 ሺህ 655 የደሃ ደሃ አርሶ አደሮች የምግብ እርዳታ በየወሩ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል።

ለከተማዋ አርሶ አደሮች የግብዓትና የቴክኖሎጂ አቅርቦት እየተካሄደ መሆኑን ተናግረው፤ በቀጣይም ምርታማነትን የሚያሳድጉ ሌሎች ድጋፎች እንደሚደረጉ ጠቁመዋል። የውሃ ፓምፕ የተሰጣቸው አርሶ አደሮች በበኩላቸው ለተደረገላቸው ድጋፍ ከተማ አስተዳደሩን አመስግነዋል።

ከከተማዋ እድገት ጋር አርሶ አደሮቹ እንዲያድጉ ለማስቻል የከተማ አስተዳደሩ የሚሰራውን ስራ አድንቀዋል። የተደረገላቸው የውሃ ፓምፕ ድጋፍ የበለጠ ለማምረት እንደሚያስችላቸውም አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል። (ምንጭ-ኢዜአ)

Related Post