አርእስተ ዜና
Sat. Apr 27th, 2024

ወጋገን ባንክ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ አገኘ

Dec12,2023
ወጋገን ባንክ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ አገኘወጋገን ባንክ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ አገኘ

ወጋገን ባንክ እ.ኤ.አ ሰኔ 30 በተጠናቀቀው የ2022/23 በጀት ዓመት በታሪኩ ከፍተኛ ሆኖ የተመዘገበውን ብር 7 ቢሊዮን ገቢ አገኘ፡፡

ህዳር 29 ቀን 2016 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሒልተን ሆቴል በተካሄደው 30ኛ መደበኛ የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባዔ ላይ እንደተገለፀው ባንኩ እ.ኤ.አ በ2021/22 በጀት ዓመት ካስመዘገበው ገቢ ጋር ሲነፃፀር የ36 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን እና ይህም ባንኩ ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች ተቋቁሞ ያስመዘገበው ከፍተኛ ገቢ መሆኑን የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አብዲሹ ሁሴን ተናግረዋል፡፡ በተያያዘም ወጋገን ባንክ በበጀት ዓመቱ ከታክስ በፊት በታሪኩ ከፍተኛ ሆኖ የተመዘገበውን ብር 1.2 ቢሊዮን ትርፍ ያገኘ ሲሆን አፈጻጸሙ ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ109 በመቶ ብልጫ አለው፡፡

በተጨማሪም እ.ኤ.አ በ2021/22 በጀት ዓመት 3.4 ቢሊዮን የነበረው የባንኩ የተከፈለ ካፒታል በ2022/23 በጀት ዓመት መጨረሻ ላይ የ17 በመቶ እድገት በማሳየት ብር 4 ቢሊዮን የደረሰ ሲሆን፤ ጠቅላላ ካፒታሉም ከአምናው ከብር 5.6 ቢሊዮን በ23 በመቶ በማደግ ብር 6.9 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ሀብትም በበጀት ዓመቱ የ24 በመቶ እድገት በማስመዝገብ ከብር 43.1 ቢሊዮን ወደ ብር 53.5 ቢሊዮን አድጏል፡፡

በበጀት ዓመቱ ባንኩ የሰበሰበው ተቀማጭ ገንዘብ እ.ኤ.አ በ2021/22 በጀት ዓመት ከተመዘገበው ብር 33.9 ቢሊዮን ሲነፃፀር የ26 በመቶ ዕድገት በማሳየት በ2022/23 በጀት ዓመት ብር 42.8 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ የብድር መጠኑም በ2021/22 ከነበረው ብር 30.3 ቢሊዮን የ32 በመቶ ዕድገት በማሳየት ወደ ብር 39.9 ቢሊዮን ማደጉን የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢው ጨምረው ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም ባንኩ በሀብት ማሰባሰብ እና የቴክኖሎጂ አቅሙን በማሳደግ በዲጂታል ዘርፍ የሚሰጡ የባንክ አገልግሎቶች እንዲሁም ሌሎች ተጓዳኝ ስራዎችን ለማዘመን ተግቶ እየሰራ መሆኑን ተናግሯል፡፡

Related Post