አርእስተ ዜና
Fri. Apr 26th, 2024

በኦሮሚያ የድርቅ ተጎጂዎች ከ68 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ ተደረገ

Feb26,2022
በኦሮሚያ የድርቅ ተጎጂዎች ከ68 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ ተደረገበኦሮሚያ የድርቅ ተጎጂዎች ከ68 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ ተደረገ

የገቢዎች ሚኒስቴርና የጉምሩክ ኮሚሽን በዛሬው ዕለት ለኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በድርቅ ለተጎዱ ወገኖች ከ68.7 ሚሊየን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የተለያዩ ቁሳቁሶች ድጋፍ ማድረጋችሀዉን የገቢዎች ሚኒስቴር ገለጸ፡፡

ድጋፉን ያስረከቡት የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ ባስተላለፉት መልእክት የገቢዎች ሚኒስቴርና የጉምሩክ ኮሚሽን እንደ ወትሮው ሁሉ የህዝብን ሃብት ለህዝብ በሚል መርህ በክልሉ በተከሰተው ድርቅ ለተጎዱ ወገኖች የሚውል የተለያዩ የምግብ ነክ ቁሳቁሶች፣ አልባሳት እና ለእንስሳት መኖ ድጋፍ መደረጉን ገልጸው ችግሩን ለመፍታት በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግም ጠቅሰዋል፡፡



በገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ ስርአት ዘርፍ ሚኒስቴር ዲኤታ አቶ ተስፋየ ቱሉ እና የታክስ ኦፕሬሽን ዘርፍ ሚ/ዴኤታ ወይዘሮ መሰረት መስቀሌ በርክክቡ ላይ እንደተናገሩት በክልሉ በተከሰተው ድርቅ ለችግር የተዳረጉ ዜጎቻችንን ከችግሩ እስኪላቀቁ ድረስ ድጋፉን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለው ህብረተሰቡ እንዲበረታና እርስ በእርሱ ተደጋግፎ ይህንን ችግር እንዲወጣም ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

ድጋፉን የተረከቡትና በኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዘዳንት ማእረግ የግብርና ክላስተር አስተባባሪ የሆኑት አቶ አብዱራህማን አብደላ በበኩላቸው ዘንድሮ በክልሉ የተከሰተው ድርቅ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸው ክልሉ ባደረገው ጥሪ መሰረት ህዝባችንን ለመታደግ ሁለቱም ተቋማት እንደተለመደው ላደረጉት ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡



ኃላፊው አክለውም ድጋፉ ለተጎጂዎቹ በፍትሃዊነት እንዲደርስ ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው ሌሎች ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችም ተጎጂዎቹ ከዚህ ችግር እስከሚወጡ ድረስ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ የተደረገው ድጋፍ ለአራት የክልሉ ዞኖች የሚከፋፈል እንደሆነ በርክክቡ ወቅት ተጠቁሟል፡፡

Related Post