አርእስተ ዜና
Mon. May 13th, 2024

የአዘዞ ጭልጋ የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ 85 በመቶ ተጠናቋል

Aug23,2022
የአዘዞ ጭልጋ የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ 85 በመቶ ተጠናቋል
የአዘዞ ጭልጋ የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ 85 በመቶ ተጠናቋል

የአዘዞ ጭልጋ የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመር እና ማከፋፈያ ጣቢያ ፕሮጀክት ግንባታ 85 በመቶ መድረሱን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የአዘዞ ጭልጋ ፕሮጀክት ጽ/ቤት ገለፀ።

የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ዳንግብጹ መንገሻ እንደገለፁት በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ ወሳኝ ሥራዎች የሚባሉት የኤሌክትሪክ ተሸካሚ ምሰሶ ተከላ፣ የማስተላለፊያ ገመድ ዝርጋታ፣ የማከፋፈያ ጣቢያው የውስጥ አጥር እና የአፈር ምለሳ ሥራዎች በመከናወን ላይ ይገኛሉ።

ለመስመር ዝርጋታው ከሚያስፈልጉት 105 የኤሌክትሪክ ተሸካሚ ምሰሶዎች ውስጥ 89 ያህሉ መጠናቀቃቸውን የገለፁት አስተባባሪው በካሳ ክፍያና ተያያዥ ጉዳዮች የዘገዩ የማስተላለፊያ መስመር የመሰረት ግንባታ፣ የምሰሶ ተከላና የዝርጋታ ሥራዎች በቀጣይ የሚሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡

ፕሮጀክቱ 43 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ባለ 230 ኪሎ ቮልት የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር እና አንድ ባለ 230/33 ኪሎ ቮልት አዲስ የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያ ግንባታን የሚያጠቃልል ነው፡፡

የአዲስ የማከፋፈያ ጣቢያ ግንባታ ግንባታ በጭልጋ፣ በነባሩ የአዘዞ ማከፋፈያ ጣቢያ ውስጥ ደግሞ ማስፋፊያ እየተከናወነ ሲሆን የጭልጋ ማከፋፈያ ጣቢያ የመጀመሪያ ሙከራ እየተደረገለት መሆኑንም አስተባባሪው ጠቁመዋል።

የአዘዞ ጭልጋ የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያና ማከፋፈያ ጣቢያ ፕሮጀክት በአካባቢው የነበረውን ከፍተኛ የኃይል መዋዠቅና መቆራረጥ ከማስቀረት አልፎ ለአካባቢው የኢንቨስትመንት መስፋፋት በር እንደሚከፍት እና በተደጋጋሚ የሚነሳውን የኃይል አቅርቦት ጥያቄ እንደሚፈታ ተስፋ ተጥሎበታል፡፡

የፕሮጀክቱን ግንባታ ሲኖ ኃይድሮ ኮርፖሬሽን የተባለው የቻይና ኩባኒያ ሲያከናውን በአማካሪነት ደግሞ ኢ.ኤል.ሲ. (ELC) የተባለ የጣሊያን ኩባኒያ እየተሳተፈበት ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ በ780 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ጭልጋ ወረዳ በአንጓባ ቡላድጌ ቀበሌ ይገኛል፡፡

Related Post