አርእስተ ዜና
Sat. Apr 27th, 2024

ለሁለት መቶ ግብር ከፋዮች ሽልማት ተሰጠ

Sep18,2020
ለሁለት መቶ ግብር ከፋዮች ሽልማት ተሰጠለሁለት መቶ ግብር ከፋዮች ሽልማት ተሰጠ

የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በተገኙበት ለሁለት መቶ ግብር ከፋዮች የፕላቲኒየም፣ የወርቅና የብር ሽልማት ተሰጠ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ሽልማቱን በሰጡበት ወቅት፤ “ለታማኝ ግብር ከፋዮች ልዩ አገልግሎት በመስጠት ቁጥራቸው እንዲበራከት በአሰራራችን ውስጥ ይካተታል” ብለዋል፡፡የገቢዎች ሚኒስቴርም ከተቋማት ጋር በመናበብ የታመኑትን በማክበር አርአያ እንዲሆኑና ያልታመኑት እንዲታመኑ ታመኝ ግብር ከፋዮች የቅድሚያ አገልግሎት የሚያገኙበትና የሚበረታቱበት መንገድ ማመቻቸት እዳለበት አቅጣጫ ሰጥተዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሸላሚ ግብር ከፋዮችን “የኢትዮጵያ ጀግኖች” በማለት የገለፁዋቸው ሲሆን የሀገር ሰላም እንዲረጋገጥና ለኑሮ ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር በርካታ ቁጥር ያለው ታማኝ ግብር ከፋዮች ሊኖሩ ይገባል ብለዋል፡፡ ግብሩን በታማኝነት የከፈለን የማክበር ባህል በማዳበር የማይከፍሉትን ወደ ታማኝ ግብር ከፋይነት ለማምጣት በመንግስት በኩል ትኩረት እንደሚሰጠው ገልፀዋል፡፡

በሌላ በኩል ለሀገራቸው የሚተጉ እንዳሉ ሁሉ ከዚህች ድሃ ሀገር የሚሰርቁ ሰዎች በመንግስት ስርዓት ውስጥ ተሰግስገው ይገኛሉ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ፡፡
የእነዚህ ሰዎች ቁጥር እንዲቀንስና እና ወደፊትም ሌብነትን የሚጠየፍ የህዝብ አገልጋይ እንዲፈጠር እጅ መንሻ የሚሹትን አሳልፎ መስጠት ከግብር ከፋዮች ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ጥቆማ በመስጠት ሌብነትን የሚዋጉ ግብር ከፋዮች ከሚከፍሉት ግብር ተቀናሽ ማድረግ ለመጀመር የገቢዎች ሚኒስቴር ጥናት እንዲያደርግ ጠቁመዋል፡፡

ግብር መክፈልና ስርቆትን መዋጋት ጎን ለጎን ማስኬድ ካልተቻለ የተሰበሰበው ገቢ በትክክል ስራ ላይ መዋሉን ማረጋገጥ አይቻልም ነው ያሉት፡፡ በዛሬው ዕለት በዩኒቲ ፓርክ የተዘጋጀው የፌደራል ግብር ከፋዮች ሽልማት ሁለተኛው ዙር ሲሆን በ2011 ዓ.ም ሐምሌ ወር የመጀመሪያው የሽልማት ስነ-ስርዓት መካሄዱ ይታወሳል፡፡

Related Post