አርእስተ ዜና
Sat. Apr 20th, 2024

1.2 ሚሊዮን ሰዎችን ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ የሚከላከል ፕሮጀክት ይፋ ሆነ

Jul23,2020
1.2 ሚሊዮን ሰዎችን ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ የሚከላከል ፕሮጀክት ይፋ ሆነ

በግል የንግድ ዘርፍ ፣ በመንግስት እና በመንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች መካከል የተመሰረተው ጥምረት በዛሬው እለት የኮቪድ-19 ወረርሽኝ የሚያስከትለውን ከፍተኛ አደጋ ለመከላከል የሚያስችል ለሚቀጥሉት ቀጣይ ወራት የሚሰራ እና እስከ 6 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወጪ ሊኖረው የሚችል ጤናችን በእጃችን! የተሰኘው ፕሮጀክት ይፋ ተደረገ።

ፕሮጀክቱ የውሃ ፣ የሳሙና እና ሌሎች ተመሳሳይ ተግዳሮቶች እጥረት የሚያጋጥማችውን እና በጣም ጥቅጥቅ ያሉ የመኖሪያ አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ የከተማዋ ነዋሪዎችን ለማገዝ ብሎም ራሳቸውን ከወረርሽኙ እንዲጠብቁ የሚያስችል ይሆናል። የፕሮጀክቱ አባል የሆኑት አምራች ኩባንያዎች በፕሮጀክቱ የመጀመሪያዎቹ 6 ወራት ውስጥ ትርፍን መሰርት ያላደረገ ስራ ለመስራት እና ሰራተኞቻቸውን በስራ መደብ ላይ ለማቆየት ተስማምተዋል። ይሄንን ለማካካስ ጥምረቱ ለተሳታፊ ኩባንያዎች ወሳኝ ከሆኑ ጥሬ ዕቃዎች እና ከማምረት ጋር ለተያያዙ የክንዋኔ ወጪዎችን የሚሸፍን ይሆናል።

ጤናችን በእጃችን! ፕሮጀክት በይፋ መጀመርን ተከትሎ ይህ አዲስ ጥምረት የፊት ጭምብሎችን እና ሳሙናዎችን የማምረት እና ማሰራጨት፣ የውሃ ገንዳዎችን መትከል ፣ ብሎም የባህሪ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ የግንዛቤ ለውጥ ፈጣሪ ትምህርቶችን ለ1.2 ሚሊዮን ለሚሆኑ ከፍተኛ ተጋላጭ ተበለው ለተለዩ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የኮቪድ-19 ወረርሽኝን የመከላከል ስራን በሚያጠናክር መልኩ የሚያደርስ ይሆናል።

ዳልበርግ ግሩፕ እና ሮሃ ግሩፕ ተነሳሽነት በመውሰድ በሀገሪቱ በአሁኑ ጊዜ ያለውን የወረርሽኝ የመከላከል ብሔራዊ ምላሽ ላይ ዘላቂ ተፅእኖ ለመፍጠር በሚያስችል መልኩ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የግል እና የመንግስት ተቋማት በጋራ በማደራጀት ወደ ስራ ገብተዋል። የፕሮጀክቱ የሙከራ ጊዜ የሚያስፈልገውን 1 ሚሊዮን ዶላር በሮሃ ግሩፕ በኩል የተገኘ ሲሆን ቀሪው 5 ሚሊዮን ዶላር ከለጋሽ ድርጅቶች ፣ የግሉ ዘርፍ እና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች የሚሰበሰብ ይሆናል። ጥምረቱ የንፅህና መጠበቂያ የሆኑ ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን ማምረትና በጣም ተጋላጭ ለሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎች በማከፋፈል በአይነቱ ለየት ያለ የንግድ ስራ ሞዴሎችንም ማስተዋወቅ ችሏል።

መንግሥት በበኩሉ በፋይናንስ ሚኒስቴር በኩል ለፕሮጀክቱ የሚመረቱ ዕቃዎች ላይ የተጨማሪ እሴት ታክስን ያነሳ ሲሆን፣ ዓላማውም የግል ተቋማት በኮቪድ-19 ላይ ለሚደረገው የመከላከል ስራ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበርክቱ ለማስቻል ነው ፡፡

ፕሮጀክቱ እስካሁን ድረስ 15 የሚሆኑ አገር በቀል በማምረቻ ዘርፍ የተሰማሩ ኩባንያዎችን በአንድ ላይ በማሰባሰብ አነጋግሯል። ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና ሴቭ ዘ ችልድረን በጎ አድራጊ ድርጅት ጋር በጋራ ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል::

የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር የከንቲባ ጽ/ቤት ውስጥ ብሎክን መሰረት ያደረገ የማህበረሰብ አደረጃጀት ኤጀንሲ በከተማው ውስጥ የሚገኙ 24,934 አካባቢዎችን በመለየት የሚገኙበትን ጊዜያዊ ሁኔታ መረጃ ሰብስቦ አዘጋጅቷል።

በተጨማሪም በ10 ክፍለ ከተማዎች የሚገኙ 121 ወረዳዎች ውስጥ 1,357 የተደራጁ ማእከላትን በመጠቀም የፊት ጭንብሎችን እና ሳሙናዎችን ለከፍተኛ ተጋላጭ ተበለው ለተለዩ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የሚያከፋፍል ይሆናል። በተጨማሪም ሴቭ ዘ ችልድረን ለጥምረቱ የቴክኒክ ድጋፍ ፣ መመሪያ እና የህብረተሰቡ ተሳትፎን በተመለከተ ድጋፍ ይሰጣል። የሚሰራጨው በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የፀደቁ የእጅ መታጠብ ፣ የፊት ጭንብል መልበስ እና አካላዊ ርቀት መጠበቅን የሚመለከቱ መልዕክቶችን ያካትታል ፡፡ የሰራተኞቹን እና የህብረተሰብ አካላትን ጤና እና ደህንነት ለመጠበቅ
ከ260 በላይ የክፍለ ከተማና የወረዳ ቡድን አመራሮችም ስልጠና ተሰጥቷቸዋል።

በተያያዘም ሜሪ ጆይ ፕሮጀክቱ የሙከራ ጊዜውን ጨርሶ ሙሉ በሙሉ ከመጀመሩ በፊት የፈንድ አስተዳደርና የስራ ሂደት ለመቆጣጠር የፕሮጀክቱን ውጤታማነት ለመገምገም ከጥምረቱ ጋር አብሮ የሚሰራ ይሆናል።

“የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ማህበረሰባችን ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት ለመከላከል የበኩላችንን ማድረግ በመቻላችን ከፍተኛ ደስታ ይሰማናል። ጥምረቱን የተቀላቀሉና ሃላፊነታቸውን በመወጣት አዳዲስ መፍትሄዎችን በማምጣት ይሄን አስቸጋሪ ጊዜ ለማለፍ አብረውን እየሰሩ ያሉትን አጋሮቻችንን እናመሰግናለን” ብለው የጥምረቱ መስራቾች ተናግረዋል። አክለውም ይህ ጥምረት ወረርሽኙን ለመዋጋት የሚያስፈልገውን ቁሳቁሶች ብሎም የባህሪ ለውጥ ትምህርት ድጋፍ የሚሰጥ ሲሆን ሌሎችም በንግዱ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች እና ተቋማት ይሄን ጥምረት በመቀላቀል የበኩላቸውን እንዲያደርጉ
ጥሪ እናቀርባለን።

ፍሰሃ አለማየሁ የፍሪ ዞን ኢንተርናሽናል ዋና ስራ አስኪያጅ በበኩላቸው “የጥምረቱ አባል በመሆናችን የማምረት ስራችን ሳይስተጓጎል በሃገራችን ውስጥ ኮቪድ-19 ወረርሽኝ የመከላከል እንቅስቃሴ እንድንደግፍ አስችሎናል” ብለው ተናግረዋል።

Related Post