አርእስተ ዜና
Thu. Apr 25th, 2024

ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ተያዙ

Sep7,2020
ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ተያዙከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ተያዙ

ጠቅላላ ግምታዊ ዋጋቸው ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የሆኑ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ከነሐሴ 21 እስከ 28/2012 ዓ.ም ባሉት ቀናት በተለያዩ የጉምሩክ መቆጣጠሪያ ጣቢዎች በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡

በተጨማሪም በብሔራዊ ባንክ ፍቃደ ያላገኘ 2000 የአሜሪካን ዶላር በመንገደኛ እጅ ተገኝቶ የተወረሰ ሲሆን ለግለሰብ የማይፈቀዱ እና ለሀገር ደህንነት ስጋት የሆኑ ካሜራ የተገጠመላቸው ሰዓት፣ መነፅርና በድብቅ የሚቀርፁ የግድግዳ ካሜራዎች እንዲሁም የስናይፐር ክፍሎች በቦሌ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ወደ ሀገር ለማስገባት ሲሞከር በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡

በህገወጥ መንገድ ከሱማሌላንድ በቶጎውጫሌ አድርጎ ሊገባ የነበረ ግምታዊ ዋጋ ያልወጣለት መጠኑ 4.5 ኪ.ግ የሆነ ማዕድን ተይዟል፡፡ ከተጠቀሰው ጠቅላላ ግምታዊ ዋጋ ውስጥ 12 ሚሊዮን ብር የሚገመተው በህገ-ወጥ መንገድ የጉምሩክ ክልልን በመግባታቸው በጋላፊ ጉምሩክ ቅ/ፅ/ቤት የተያዙ ተለያየ ሞዴል ያላቸው አምስት ተሽከርካሪዎች ናቸው፡፡

የኮንትሮባንድ ዕቃዎቹ በቁጥጥር ስር የዋሉት በፍተሻ፣ ጫካ እና ቤት ውስጥ ተከማችተው በጥቆማ ተደርሶባቸው፣ በከባድ ጭነት ተሽከርካሪ ባለ 40 ጫማ ባዶ ኮንቴነር ውስጥ ተደራቢ ላሜራ በውስጥ በኩል በማዘጋጀት ባዶ ኮንቴይነር በማስመሰል ለማለፍ ሲሞከር ነው፡፡

የተያዙት ዕቃዎች የህዝብ ጤንነት እና ሰላም አደጋ ላይ የሚጥሉ፣ ህጋዊ የንግድ ውድድርን የሚያዛቡ የጦር መሳሪያዎች፣ መድኃኒቶች፣ አደንዛዥ እፆች፣ ኤሌክትሮኒክሶች፣ የተሽከርካሪ ጎማ እና ልዩልዩ ምርቶች ናቸው፡፡

የኮንትሮባንድ ዕቃዎቹ በቁጥጥር ስር በዋሉበት ወቅት በዝውውሩ እጃቸው ሊኖርበት ይችላል ተብለው የተጠረጠሩ ግለሰቦች ምርመራ እየተደረገባቸው ይገኛል፡፡
ለሀገር ሰላም፣ ለህዝብ ጤናና ደህነት ቅድሚያ ሰጥታቸው ይህንን ውጤታማ የኮንትሮባንድ መከላከል ስራ የሰራችሁ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የምትገኙ የጉምሩክ ሰራተኞች እና አመራሮች፣ የፀጥታ አካላት እና በጥቆማ የተሳተፋችሁ ዜጎች በሙሉ የገቢዎች ሚኒስቴር ምስጋናውን ያቀርባል፡፡

በተጠቀሰው ጊዜ ከብር 5 ሚሊዮን በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው ሲጋራ እና ሺሻ የነዳኝ መኪና ታንከር ውስጥ በመደበቅ ለማሳለፍ ሲሞከር በአዋሽ ጉምሩክ ቅ/ጽ/ቤት በቁጥጥር ስር መዋሉ የሚታወስ ነው፡፡
(ምንጭ -የገቢዎች ሚኒስቴር)

Related Post